1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በኢትዮጵያ ፖለቲካ ምህዳር የኦፌኮ-ኦነግ ጥምረት

ሐሙስ፣ ነሐሴ 11 2015

የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ) ና የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) በቀጣይ ምርጫ ላይ በመሳተፍ ለአገሪቱ ፖለቲካ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከት በጥምረት ለመስራት እንደሚንቀሳቀሱ አውስተዋል ፡፡“ጠባብ የፖለቲካ ምህዳር ተስተውሏል” ያሉት የፖለቲካ ድርጅቶቹ አሁንም ይባሱኑ ምህዳሩ እጅጉን ጠቧል ሲሉ ያማርራሉ፡፡

https://p.dw.com/p/4VI1P
የኦሮሚያ ክልል መልክዓ ምድር
የኦሮሚያ ክልል መልክዓ ምድር

በ2013 ዓ.ም. ብሔራዊ ምርጫ ያካሄደችው ኢትዮጵያ ሌላኛውን ቀጣይ ምርጫ ለማድረግ ከሶስት ዓመታት ያነሱ ጊዜያት ብቻ ይቀራሉ፡፡ በምርጫው ተመርጦ ስልጣን ላይ ያለው መንግስት አስቀድሞም ሆነ ከምርጫው በኋላ ባላቧራው ግጭት መፈተኑም ነው የሚነገረው፡፡ በወቅቱም ምርጫው ላይ “ጠባብ የፖለቲካ ምህዳር ተስተውሏል” በማለት ምርጫው ላይ ሳይታደሙ የቀሩት እንደ የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ) እና የኦሮሞ ነጻነት ግንባር(ኦነግ) ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች አሁንም ይባሱኑ ምህዳሩ እጅጉን ጠቧል ሲሉ ያማርራሉ፡፡ ፓርቲዎቹ በቀጣይ ምርጫ ላይ በመሳተፍ ለአገሪቱ ፖለቲካ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከት በምን አይነት መልኩ እራሳቸውን እያዘጋጁ እንደሚገኙም ተጠይቀው፤ በጥምረት ለመስራት ስምምነት ባኖሩት መሰረት እንደሚንቀሳቀሱ አውስተዋል፡፡ ይሁንና በአገሪቱ የሚስተዋሉትን ግጭት-አለመረጋጋቶችን አስታኮ የፖለቲካ ምህዳሩ ክፉኛ መጥበብ ስለምርጫ እና መሰል ትግባራት ማሰብን አስቸጋሪ ያደርግብናል እያሉ ነው፡፡

የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ) ሊቀመንብሩ ፕሮፌሰር መረራ ግጭት በተስፋፋባት ኢትዮጵያ አሁን ላይ ስለፖለቲካ ምህዳር መስፋት ማሰብ አስቸጋሪ ሆኗል ሲሉ አስተያየታቸውን ይጀምራሉ፡፡ “የፖለቲካ ምህዳሩ የዛሬ 5 ኣመት ከነበረው ጋር ስታወዳድረው በእጅጉ ጠቧል፡፡ እኛ እንኳ የዛሬ አምስት ዓመት የነበረን ቢሮዎች ብዛት 206 ነበር አሁን 3 ብቻ ነው ያለን፡፡ ተንቀሳቅሰን መስራት አንችልም፡፡ አንዱ የግጭቶችም ምንጭ እኮ ይህ ይመስለኛል” ሲሉም አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ዓርማ፦ ፎቶ ከማኅደር
በኦሮሚያም ሆነ ከኦሮሚያ ውጪ ግጭቶች ሲባባሱ እንጂ ሲረግቡ አይስተዋልም ሲል የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) የፖለቲካ ኦፊሰር ዶይቸ ቬለ ገልጿል ።ምስል Seyoum Getu/DW

በኦሮሚያም ሆነ ከኦሮሚያ ውጪ ግጭቶች ሲባባሱ እንጂ ስረግቡ አይስተዋልም ያሉት ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ፖለቲካ ደግሞ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) የፖለቲካ ኦፊሰር ቤቴ ኡርጌሳ ናቸው፡፡ አቶ ቤቴ ይህ ሁኔታ ፖለቲካ ምህዳሩን ክፉኛ አጥብቧልም ይላሉ፡፡ “ከእኛ ተነስተን ብንመለከተው ከዋና ቢሮያችን ጀምሮ አንድም ምንቀሳቀሻ የለንም፡፡ ዋና ቢሮያችን ገብተን መስራት አንችልም፡፡ 

ሌላው ወረዳ እና ዞን ላይ አይታሰብም፡፡ አመራሩም እንደታሰረ፤ ምንግስትም ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ቁች ብሎ የመነጋገር ምንም ፍላጎት ባላሳየበት ፖለቲካ ምህዳሩ አስቸጋሪ ይሆናል” ብለዋል፡፡

ሁለቱ የፖለቲካ ድርጅቶች ስለቀጣዩ ምርጫ ከወዲሁ ምን እያሰቡ ይሆን? የኦፌኮ ሊቀመንበር ፕ/ር መረራ ጉዲና አሁን እያደረግን ያለው ትግል ከሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር በመሆን የተዘጋውን የፖለቲካ ምህዳር የማስከፈት ጥረት ነው ይላሉ፡፡ “በሚገፋበት መንገድ ምርጫ ብቻ እያሉ በየአምስት ዓመት በተለመደው መንገድ መሄድ ትርጉም የለውም፡፡ እውነተኛ ምርጫ መደረግ አለበት፡፡ እኛን መንግስት የሚገፋን ሆን ብሎ በክልሉ ያለንን ሰፊ ተሰሚነት ስለሚያውቅ ነው፡፡” 

ፕሮፌሰር መረራ የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ ሊቀመንበር፦ ፎቶ ከማኅደር
ፕሮፌሰር መረራ ቀጥለውም በቀጣዩ ምርጫም ከኦነግ ጋር በጋራ ለመስራት በስምምነታችን መሰረት እንቀሳቀሳለን ይላሉ፡፡ ፕሮፌሰር መረራ በ2013ቱ ምርጫ እኩል እጩዎችን በጋራ ከማቅረብ ጀምሮ በትብብር አብሮ ለመስራት ስምምነት ማኖራቸውንም አስታውሰው፤ ሁለቱ የፖለቲካ ድርጅቶች የሰፋ የርዕዮት ልዩነት እና ዓለማ እንደሌላቸውም አስረድተዋል፡፡ምስል Seyoum Getu/DW

ፕሮፌሰር መረራ ቀጥለውም በቀጣዩ ምርጫም ከኦነግ ጋር በጋራ ለመስራት በስምምነታችን መሰረት እንቀሳቀሳለን ይላሉ፡፡ ፕሮፌሰር መረራ በ2013ቱ ምርጫ እኩል እጩዎችን በጋራ ከማቅረብ ጀምሮ በትብብር አብሮ ለመስራት ስምምነት ማኖራቸውንም አስታውሰው፤ ሁለቱ የፖለቲካ ድርጅቶች የሰፋ የርዕዮት ልዩነት እና ዓለማ እንደሌላቸውም አስረድተዋል፡፡ ምናልባት ምቹ ሁኔታዎች ወደ ፊት ሲፈጠሩና ሁለቱን የፖለቲካ ድርጅቶች የሚለያቸው ነትብ ሲጠብ አንድ ፓርቲ የመሆን እድልም እንዳለ ጠቁመዋል፡፡

ሌላኛው ፖለቲከኛ አቶበቴ ዑርጌሳ ግን አሁን ላይ ያለው የፖለቲካ ሁናቴ ስለውህዴትና ግንባር ብሎም ስለምርጫ ማሰብ እንኳ የማያስችል ነው ይላሉ፡፡ “በርግጥ ሁለታችንም በጋራ ለመስራት ጥረት ስናደርግ ነበር፡፡ አሁን ባለው የፖለቲካ ድባብ ግን ምንም ነገር ማሰብ ቅንጦት እየመሰለን ነው፡፡ ምክኒያቱም በግጭት አለመረጋጋቱ በየቀኑ ግድያና መፈናቀል ነው ያለው፡፡” 

ሁለቱ አንጋፋ የፖለቲካ ድርጅቶች በተለይም በኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ ተሰሚነት እንዳላቸው ይታመናል፡፡ ፓርቲዎቹ በባለፈው ምርጫ የአመራሮቻችና አባላቶቻቸው እስራት እንዲሁም የፖለቲካ ምህዳር በተለያዩ ድርጊቱ በክልሉ መጥበብን በምክኒያትነት አንስተው እራሳቸውን ከምርጫው ማግለላቸው ይታወሳል፡፡

ሥዩም ጌቱ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

አዜብ ታደሰ